ለባለሥልጣኑ አመራሮችና ሠራተኞች የባህሪያዊ እና የቴክኒካል የብቃት ምዘና ላይ ያተኮረ የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠና ተሰጠ
ለተከታታይ ሁለት ቀናት ከህዳር 23 እስከ 24 ቀን 2018 ዓ.ም በባለሥልጣኑ መሰብሰቢያ አዳራሽ የተሰጠውን የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠና በንግግር የከፈቱት የባለሥልጣኑ የእውቅና እና ስታንዳርዳይዜሽ ዘርፍ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ዶ/ር ድንኳና ንጉሳ በሀገር አቀፍ ደረጃ የሚደረገው የተቋማት ሪፎርም ከዚህ ቀደም በሀገሪቱ ከታዩት ሪፎርሞች የተለየ እና የተሻለ ውጤት ያመጣል ተብሎ የሚጠበቅ መሆኑን በመግለጽ የባለሥልጣኑ ሠራተኞች ሪፎርሙን በግልጽ ተረድተው፣ በቂ ግንዛቤ አግኝተው እና የራሳቸው አድርገው ከተንቀሳቀሱ ትልቅ ተቋማዊ ለውጥ ሊያመጡ የሚችሉ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ለባለሥልጣኑ ዓላማ ፈጻሚ አመራሮችና ባለሙያዎች የቴክኒካል ብቃት ምዘናን በተመለከተ የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠና የሰጡት የአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ዶ/ር ደረጀ እንግዳ በበኩላቸው በባለሥልጣኑ ዓላማ ፈጻሚ የሥራ ክፍሎች የሚሰሩ ሥራዎች በቴክኒካል ብቃት ምዘና ስርዓት ውስጥ ስለሚኖራቸው እይታ እና ሥራዎችን አቀናጅቶና አሰናስሎ መስራት ትልቅ ውጤት ለማስመዝገብ ከፍተኛ ሚና እንዳለው በአደረጉት ሰፊ ማብራሪያ እና ገለጻ አስረድተዋል ፡፡ በባለሥልጣኑ የስታንዳርዳይዜሽን እና ብቃት ማእቀፍ መሪ ሥራ አስፈጻሚና የሪፎርም ኮሚቴው ሰብሳቢ ዶ/ር ሀብታሙ ተሾመ በፌደራል ሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን የተዘጋጀውን የባህሪያዊ እና የቴክኒካል ምዘና ማእቀፍ በተመለከተ ባቀረቡት ገለጻ ላይ ብቃት ማለት ከምንሰራው ሥራ አንጻር ሊታይና ለሚዘን የሚችል መሆኑና የሪፎርሙ ዓላማ የሠራተኞችን የአቅም ዝግጁነት መለካት በመሆኑ ብቁ ሆኖ መገኘት አስፈላጊ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የቀረቡትን መነሻ ሀሳቦች መሠረት በማድረግ በተደረገው ውይይት ላይ ለተነሱ ሐሳብ አስተያየት እና ጥያቄዎች በባለሥልጣኑ የእውቅና እና ስታንዳርዳይዜሽ ዘርፍ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ዶ/ር ድንኳና ንጉሳ፣ በአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ፕሬዝዳንት ዶ/ር ደረጀ እንግዳ እና በሪፎርም ኮሚቴው ሰብሳቢ ዶ/ር ሀብታሙ ተሾመ ምላሽና ማብራሪያ ተሰጥቶ የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠናው ተጠናቋል፡፡ የኢፌዲሪ ትምህርትና ስልጠና ባለሥልጣን በፊስቡክ -https://www.facebook.com/FDRE.ETA በትዊተር- https://twitter.com/FDRE_ETA በቴሌግራም -https://t.me/FDRE_ETA በዌብሳይት Www. neta.gov.et ይከታተሉ ።
